ምናልባት አንድ ቀን...

እያወቅን ወደን የምንከርምበት ዓለም አለ። ድንገት የሆነ ቀን ከእጃችን እንደሚነጠቅ እያወቅንም “እስቲ እግዜር ያውቃል“ ብለን በደስታችን ውስጥ እንሰነብታለን። እግዜር ያውቃልን ዛሬ ለመቁረጥ ስንቸገር፥ ለመወስን ስንወላውል ለራሳችን የምንሰጠው ማስተባበያ እናደርገዋለን። እግዜር ወዶ መለያየት እንዳለ፥ ፈልጎ ማጣት እንዳለስ የሚያውቅ አይደለምን?

ሁሉም ሲያልፍ ትላንት በቀልባችን ውስጥ የማይነቀል ችካል ተክሎ ያሰቃየናል። ትዝታ ምስኪኖችን ከማሰቃየት ውጪ ሌላ ሥራ የለውም። ሕመም ተጠይፈን የጠጣናቸው መድኃኒቶች ሌላ የማይሽር ሕመም ይሰጡናል።መንገድ ተጠይፈን የወሰድናቸው አቋራጮች ሌላ ረጅም መንገድ ያነጥፉልናል።ብቸኝነትን ተጠይፈን የታቀፍናቸው ገላዎች የማያልቅ ብቸኝነት ጥለውብን ያልፋሉ። ማንንም ያለመውደድን ባዶነት የወደድነውን በመናፈቅ ባዶነት የምንለውጥ ምን ያለን ሞኞች ኖረናል!?
ገጽ 129

ርዕስ፡ ምናልባት አንድ ቀን...
ደራሲ፡ ሄኖክ በቀለ ለማ